ለሁለት ሳምንታት ያህል በሳንባ ምች ህመም ህክምና ላይ ያሉት የሮማ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳስ ፖፕ ፍራንሲስ የመተንፈስ ችግር እንዳጋጠማቸው ቫቲካን አስታወቀች።
ያጋጠማቸው የመተንፈስ ችግር ከህመማቸው ጋር የማይያዝ እንደሆነም ቫቲካን ገልጻለች።
አርብ ዕለት ሳል ካጋጠማቸው በኋላ ተከታታይ ማስታወክ እና ድንገተኛ የመተንፈስ ችግር ገጥሟቸዋል ተብሏል።
የ88ቱ ዓመት አዛውንት ካጋጠማቸው ትውከት በኋላ ሳንባቸው ላይ ያለው እርጥበት መመጠጥ እንደነበረበት ተገልጾ አሁን ለመተንፈስ የሚያግዛቸው ጋዝ በፊት ጭምብል ተገጥሞላቸዋል።
የቫቲካን ምንጮች እንደተናገሩት ፖፑ ባጋጠማቸው የመተንፈስ ችግር የከፋ ሁኔታ ገጥሟቸው እንደሆነ ለማወቅ ዶክተሮቻቸው ከ24- 48 ሰዓታት ያስፈልጋቸዋል ብለዋል።
ዶክተሮቻቸው በአሁኑ ወቅት ስለ ፖፑ ሁኔታ ከመናገር ተቆጥበዋል።
ፖፕ ፍራንሲስ ንቁ እንደሆኑ "በጥሩ መንፈስ" ላይ እንደሆኑ ምንጮቹ ይናገራሉ።
"ቅዱስ አባታችን የመተንፈሻ አካላት ፊዚዮቴራፒ ካደረጉ በኋላ ሳል ያጋጠማቸው ሲሆን ይህም ተከታታይ ትውከት እንዲሁም ድንገተኛ በሆነ ሁኔታ የመተንፈስ ችግር አስከትሎባቸዋል" ብሏል ቫቲካን ባወጣችው መግለጫ።
ይህንንም ተከትሎ የመተንፈሻ መሳሪያ እንደተገጠመላቸው መግለጫው አክሏል።
የቫቲካን ምንጮች እንደተናገሩት ፖፕ ፍራንሲስ ያጋጠማቸው የመተንፈሻ ችግር በአገሬው ሰዓት አቆጣጠር ከሰዓት ስምንት ሰዓት ላይ አካባቢ ቢሆንም፤ ለምን ያህል ጊዜ እንደቆየባቸው ከመግለጽ ተቆጥበዋል።
ከጥቂት ቀናት በፊት ፖፕ ፍራንሲስ እየተሻላቸው እንደሆነ ቫቲካን መግለጫ አውጥታ ነበር።
ቁርባንም እንደቆረቡ ተነግሯል።
ቫቲካን የፖፕ ፍራንሲስን የጤና ሁኔታ አስመልክቶ በሰጠችው መግለጫ የመሻሻል ምልክቶች እያሳዩ ቢሆንም በሮም ጌሜሊ ሆስፒታል ይቆያሉ ብላለች።
ፖፕ ፍራንሲስ ለቀናት በኋላ ካጋጠማቸው የመተንፈስ ችግርን ተከትሎ ከሁለት ሳምንታት በፊት ነበር ወደ ጤና ማዕከል የተወሰዱት። መጀመሪያ ላይ ከመተንፈሻ ችግር በተጨማሪ በሁለቱም ሳንባዎቻቸው ላይ የሳምባ ምች መጠቃታቸው ተገልጾ ነበር።
ከቀናት በኋላ አተነፋፈሳቸው ላይ ከፍተኛ ችግር እንዳጋጠማቸው እና በ"አስጊ" ሁኔታ ላይ እንዳሉ መግለጫ ቢወጣም ባለፈው ሳምንት እሁድ የተሻለ ሁኔታ ላይ እንዳሉ ተገልጾ ነበር።
ቫቲካን ተሽሏቸዋል የሚል መግለጫ ካወጣች በኋላ በማግስቱ ፖፑ የሚመሩትን የጸሎት ፕሮግራም ለሁለት ሳምንታት ያህል ለማቋረጥ በመገደዳቸው መላው የካቶሊክ ምዕመናን እንዲጸልዩላቸው ጠይቀዋል።
የሮማው ሊቀ ጳጰስ በባለፉት አስራ ሁለት ዓመታት ቤተ ክርስቲያኗን በመሩበት ቆይታቸው በተደጋጋሚ ሆስፒታል ገብተዋል። ከሁለት ዓመታት በፊትም ከሳንባ ህመም ጋር በተያያዘ ሆስፒታል ገብተው ህክምና ተደርጎላቸዋል።
አርጀንቲናዊው ፖፕ ፍራንሲስ የሮማን ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን የመሩ የመጀመሪያው የላቲን አሜሪካ ተወላጅ ናቸው።
Comments
Leave a Comment